የቤተ ክርስቲያናችን አመሠራረት እ.ኤ.አ. ከ 1989 ዓ.ም. ጀምሮ የተወሰኑ ቅዱሳን ወንድሞችና እህቶች በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት በመሠብሠብ የተጀመረ ነው፡፡ በተለያየ ሁኔታ በጀርመን ሀገር ለመኖር ከሀገር ቤት እና ከተለያዩ ሀገሮች ጌታን የሚያውቁ እና የሚያገለግሉ የነበሩ እየበዙ እንዲሁም አዳዲስ ነፍሳትም እየተጨመሩ ኅብረቱ ተጠናከረ፡፡ በመሆኑም በሁሉ አቅጣጫ እየሰፋች በቁጥርም እየበዛች በመምጣቷ እ.ኤ.አ ከሐምሌ 27-30/ 1995 ዓ.ም. የመጀመሪያውን ዓመታዊ ታላቅ ኮንፈራንስ ከመላው የጀርመን ከተሞች ከሚገኙ ኅብረቶች ጋር በመሰባሰብ በግምት ከ 500 በላይ የሚሆኑ ቅዱሳንን ተቀብሎ በማስተናገድ በእግዚአብሔር እርዳታ የተሳካ ኮንፈራንስ አድርጋለች። ከዚህም በኋላ የኅብረቷ የምእመናን ቁጥር መጨመርና የመንፈሳዊ አገልግሎትም እየሰፋ በመምጣቱ ምክንያት በወቅቱ በነበሩት የኅብረቱ መሪዎች ኅብረቷ በመንግሥት እውቅና እንዲኖራት እ.ኤ.አ. በ 1998 ዓ.ም. በጀርመን ሀገር በኑርንበርግ ከተማ ”በኑረንበርግ የኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተ ክርስቲያን” በሚል ስያሜ ከኅብረትነት ወደ ቤተ ክርስቲያንነት ከፍ እንድትልና መንግሥታዊ ሕጋዊነትንም እንድታገኝ ሆናለች። እንዲሁም እ.ኤ.አ. በ 2000 ዓ.ም. የቤተ ክርስቲያን ምሥረታ እና የምስጋና በዓል በማድረግ እና በቀጣይም አገልግሎቷን በተደራጀ መልኩ ስታከናውን ቆይታ ቤተ ክርስቲያኒቱ ከደረሰችበት መንፈሳዊም ሆነ የገንዘብ (Financial) አቅም አንጻር ልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፎችን በማደራጀት ዲያቆናትን፣ ሽማግሌዎችን እና አንድ ወንጌላዊ በ2010 እንዲሁም ቋሚ በጀት በመመደብ አንድ የሙሉ ጊዜ አገልጋይ የሆነ መጋቢ (ፓስተር) እ.ኤ.አ. በ2006 ዓ.ም. ከሌላ ከተማ አምጥታ በጉባዔ በመጋቢነት ሾማለች።
አሁን የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕጋዊ ስያሜ “የጸጋው ቃል አማኞች ቤተ ክርስቲያን በኑርንበርግ” በመባል በኑርንበርግ ከተማ እንዲሁም “የጸጋው ቃል አማኞች ቤተ ክርስቲያን በቩርዝቡርግ” በቩርዝቡርግ ከተማ ሁለተኛ አጥቢያ እና “የጸጋው ቃል አማኞች ቤተ ክርስቲያን በሽቫይንፉርት” በሽቫይንፉርት ከተማ ሦስተኛ አጥቢያ በመትከል ቅዱሳንን ታገለግላለች፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በታላቁ ተልዕኮ አገልግሎትም ወደ ብዙዎች ወንጌል እያደረሰች የምትገኝ ቤተ እምነት ሆናለች፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን አገልግሎቶች በብዝሃ ቋንቋ (አማርኛ፣ አፋን ኦሮሞ፣ ትግርኛ እና ጀርመንኛ) ለብዙዎች ተደራሽ ሲሆን በማኅበራዊ ሚዲያም የእግዚአብሔርን የድነት መልእክት ለሰው ልጆች ሁሉ እያደረሰች ትገኛለች፡፡
ቤተ ክርስቲያናችን በአሁኑ ወቅት፡ የኢትዮጵያ ወንጌላዊያን ዐብያተ ክርስቲያናት ኅብረትን ጨምሮ የኢትዮጵያ ወንጌላውያን ዐብያተ ክርስቲያናት ኅብረት በአውሮጳ (Alliance of the Evangelical Ethiopian Churches in Europe) እና የኢትዮጵያ ወንጌላዊያን ዐብያተ ክርስቲያናት ኅብረት በጀርመን (Äthiopische Evangelische Christen Gemeinschaft in Deutschland e.V.) አባል ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡